ዜናዎች

#ባህር ዳር ከተማ 75 000 /ሰባ አምስት ሺህ/ ብር እንዲከፍሉ የዲሲፕሊን ቅጣት ተወስኖበታል !

ቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 2015 4ኛ ሳምንት በተደረጉ ስምንት ጨዋታዎች ስድስት ጨዋታዎች በመሸናነፍ ሁለት ጨዋታ በአቻ ሲጠናቀቅ በአጠቃላይ 18 ጎሎች በ14 ተጫዋቾች ተቆጥረዋል። በሳምንቱ 46 ተጫዋቾችና የቡድን አመራሮች በቢጫ ካርድ ሲገሰፁ አንድ ተጫዋች በሁለተኛ ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል።
የኢትዮጵያ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር አመራርና ስነ-ስርዓት ኮሚቴ ጥቅምት 12/2015 ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ የተደረጉ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ግጥሚያ(ዎች)ከዳኞች እና ከታዛቢዎች የቀረቡለትን የዲሲፕሊን ሪፖርት ከመረመረ በኋላ የተለያዩ ውሳኔዎችን አስተላልፏል።
በተጫዋቾች ደረጃ እንየው ካሳሁን(ድሬደዋ ከተማ) ሁለተኛ ቢጫ ካርድ የሚያስጥ ጥፋት በመፈፀሙ ቀይ ካርድ አይቶ ከጨዋታ ሜዳ ስለተወገደ 1 ጨዋታ እንዲታገድ እንዲሁም የተጋጣሚ ቡድን ተጫዋች ላይ ስለ መትፋቱ ሪፖርት ስለቀረበበት በተጨማሪ ጥፋቱ ከአንዱ ጨዋታ ሌላ በኢ.እ.ፌ ዲሲፕሊን መመሪያ መሰረት 6/ስድስት/ ጨዋታ እንዲታገድና ብር 3000 /ሶስት ሺህ / እንዲከፍል ሲወሰን ሄኖክ አየለ(ኢትዮ ኤሌክትሪክ) በጨዋታ ወቅት ሃይማኖታዊ መልእክት የሚያስተላልፍ ጽሁፍ የተጻፈበት ልብስ ከማሊያው ስር ደርቦ ስለመልበሱ ሪፖርት ተደርጎበት በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የውድድር ደንብ መሰረት ተጫዋቹ ብር 3000 /ሶስት ሺህ ብር/ እንዲሁም ክለቡ ብር 10000 /አስር ሺህ ብር/ እንዲከፍሉ ተወስኗል፡፡

በክለቦች ደረጃ ሃዋሳ ከተማ ፣ ድሬደዋ ከተማ እና ሲዳማ ቡና ባደረጉት የሳምንቱ ጨዋታ የክለባቸው የተለያዩ ከአምስት በላይ ተጫዋቾች በተለያዩ ጥፋቶች ካርድ የተሰጣቸው በመሆኑ በኢ.እ.ፌ ዲሲፕሊን መመሪያ መሰረት እያንዳንዳቸው የገንዘብ ቅጣት ብር 5000 /አምስት ሺ/ እንዲከፍሉ እንዲሁም ባህር ዳር ከተማ በሳምንቱ ጨዋታ የክለቡ ደጋፊዎች አፀያፊ ስድብ ስለመሳደባቸው፣ ያልተገባ መልዕክት ማስተላለፋቸው፣ አንድ የክለቡ መለያ የለበሰ ደጋፊ በጨዋታ ወቅት ወደሜዳ ዘሎ በመግባት ሁከት ስለማስነሳቱ ሪፖርት የተደረገ በመሆኑም ደጋፊዎቹ አፀያፊ ስድብ በመሳደባቸውና ያልተገባ መልዕክት በማስተላለፋቸው በኢ.እ.ፌ ዲሲፕሊን መሰረት ብር 50000/ሃምሳ ሺህ/ እንዲሁም የክለቡ ደጋፊ ወደሜዳ ዘሎ በመግባት ሁከትና ረብሻ በማስነሳቱ በዚሁ መመሪያ መሰረት ብር 25000 /ሃያአምስት ሺህ / በድምሩ 75 000 /ሰባ አምስት ሺህ/ እንዲከፍሉ ወስኗል፡፡