ቤትኪንግ ፕሪሜር ሊግ ዜናዎች

“ለድሬደዋ ደጋፊዎቻችን የሚገባቸውን ውጤት እየሠጠናቸው አይደለም፤ ነገር ግን በቀሩት ጨዋታዎች ለመስጠት በሚገባ እየሠራን ነው ” ➖ፍሬዘር ካሳ (ድሬዳዋ ከተማ )

የድሬዳዋ ከተማው የመሀል ተከላካይ ፍሬዘር ካሳ በድሬዳዋ ከ17ኛው ሳምንት እሰከ 21ኛው ሳምንት ሲካሄድ በነበረው የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ ድንቅ እንቅስቃሴ ሲያሳዩ ከነበሩ ተጨዋቾች አንዱ ነው ።ፍሬዘር በቅ/ዮርጊስ ክለብ ከታዳጊ ቡድን ተነስቶ እስከ ዋናው ቡድን ድረስ  የተጫወተ ሲሆን ለኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ብሔራዊ ቡድንም መጫወቱ መቻሉ የሚታወስ ነው፡፡

በ2012 ዓ.ም ደግሞ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ  ወደ ድሬ ከተማ የተቀላቀለ ሲሆን ዘንድሮ በድሬ ኮንትራቱ የተጠናቀቀ ቢሆንም ከክለቡ ጋር ባደረገው ስምምነት ለአንድ አመት ለመቆየት መስማማቱም ይታወሳል።በድሬዳዋ ከተማ ለአንድ ወር በቆየው የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ ቆይታ ጥሩ አቋም ላይ የነበረውን የመሀል ተከላካዮ ፍሬዘር ካሳን ከኢትዮኪክ ጋር አጭር ቆይታ አድርጓል እንሆ:

ኢትዮኪክ :- የዘንድሮ የክለባቹ አቋም በፍሬዘር ህይታ እንዴት ይገለጻል?
ፍሬዘር :- በመጀመሪያ ደረጃ ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች እንኳን ለብርሀነ ትንሳኤው በሰላም በጤና አደረሳችሁ እላለሁ። የክለባችን የዘንድሮው አቋም ያው እኛ ካለንበት ደረጃ አንጻር ትንሽ ጫና ውስጥ ነን ። ከዛ አንፃር አብዛኞቹ ጨዋታዎች ጫና ውስጥ ነበሩም ናቸው ማለት ይቻላል።
ኢትዮኪክ :- የድሬዳዋ የዘንድሮው ሃሳባችሁ እሰከምን ድረስ ነው?
ፍሬዘር :- ያው በቻልነው መጠን ቲሙን በሊጉ ለማቆየትና የተሻለ ቦታ ላይ ማስቀመጥ ነው።
ኢትዮኪክ :- እሱንስ እያሳካን ነው ትላለህ?
ፍሬዘር :- እየሞከርን ነው ባይ ነኝ…
ኢትዮኪክ:- በድሬዳዋ የቤትኪንግ ቆይታ እንዲሁም ዘንድሮ ጥሩ ብቃት ላይ እንደሆነክ ብዙዎች ይስማማሉ፤ በዚህ ላይ ምን የምትለኝ አለ?
ፍሬዘር :- አዎ ።በተወሠነ መልኩ መሻሻል እያሳየሁ ነው:: ይኔ ጅምር ነው ። ከዚህ በበለጠ ራሴን በሁሉም ነገር በሚገባ አዘጋጅቼ የተሻለ ሆኜ መቅረብ እፈልጋለሁ።
ኢትዮኪክ:- በድሬዳዋ በሜዳችሁ በተካሄደው ቤትኪንግ ያገኛችሁት ውጤት እንዴት ታየዋለህ ?
ፍሬዘር :- በድሬ የነበረው ቆይታችን ከአምስት ጨዋታ ሁለቱን አሸንፈን ሶስቱን አቻ ነበር የወጣነው። በአጠቃላይ ውጤቱ ተገቢ አልነበረም። ለምሳሌ በ21ኛው ሳምንት በመጨረሻው ጨዋታ በብዙ መንገድ የተሻልን ነበርን። ግን ያው እግር ኳስ አንዳንዴ እንደዚ ናት ። ጥሩ ቢኮሆነህም አንዳንዴ አታሸንፍም።
ኢትዮኪክ:- የደጋፊውን ፍላጎት እያደረግን ነው ትላለህ ?
ፍሬዘር :- ለድሬደዋ ደጋፊዎቻችን የሚገባቸውን ውጤት እየሠጠናቸው አይደለም። ነገር ግን በቀሩት ጨዋታዎች ከኛ የሚፈልጉትን ውጤት ለመስጠት በሚገባ እየሠራን ነው።
ኢትዮኪክ:- ድሬደዋ ከተማ ዘንድሮ የመውረድ ስጋትስ?
ፍሬዘር :- ቡድናችን ድሬዳዋ ከተማ አሁን ስለመውረድ ሳይሆን የቀሩንን ጨዋታዎች እንዴት ማሸነፍ እንዳለብን ነው እያሰብን ያለው። ቲሙ ያለበት ደረጃ በፍጹም አይገባውም፤ ቢሆንም ቀሪ ጨዋታዎችን ከዚ በተሻለ ተነሳሽነት በሊጉ ለመቆየት ነው የምንጫወተው።
ኢትዮኪክ:- የመጨረሻ ጥያቄያችን በ21ኛው ሳምንት የድሬደዋ የቤትኪንግ የመጨረሻ ጨዋታ ላይ አቅፈሃት ወደ ሜዳ የገባኸው ልጅህ ናት ?
ፍሬዘር :- እኔን ትመስላለች አይደል (በፈገግታ) ልጄ ብትሆን በጣም ነበር። ደስም ይለኝም ነበር። ግን አደለችም…. ( በፈገግታ ) አብሮኝ የሚጫወተው የጓደኛዬ የእህቱ ልጅ ናት።
ኢትዮኪክ:- እናመሰግናለን ፍሬዘር
ፍሬዘር :- እንግዳቹ ስላረጋችሁኝ በጣም አመሠግናለሁ።