አፍሪካ ዜናዎች

➖የኢትዮዽያ እግርኳስ ፌዴሬሽን በካሜሩኑ ውጤት የኢትዮጵያ ህዝብን ይቅርታ ጠየቀ !

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በካሜሩን ያሳየውን የነበረውን ቆይታ አስመልክቶ የቡድኑ ዋና አሰልጣኝ ውበቱ አባተ እና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ዋና ፀሀፊ አቶ ባህሩ ጥላሁን ዛሬ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
በጋዜጣዊ መግለጫው ፌዴሬሽኑ
➖“ባቀድነው ልክ በካሜሩኑ የአፍሪካ ዋንጫ ውጤታማ ባለመሆናችን የኢትዮጵያ ህዝብን ይቅርታ እንጠይቃለን” የፌዴሬሽኑ ዋና ፀሀፊ አቶ ባህሩ ጥላሁን ተናግረዋል ።
➖ አቶ ባህሩ ቀጥለው “ባለፈው የአፍሪካ ዋንጫ ሁለት ፓስፖርት ይዘው የተጫወቱ ነበሩ ይሄ ስህተት ነው መጠየቅ ያለበት ወገን መጠየቅ አለበት ያኔ ትውልደ ኢትዮጵያዊ ተጫውቷል ተብሎ አሁን የሚጠየቀው ያኔ ተገቢ ያልሆነ ድርጊት በመፈጸሙ ነው..ሚዲያው ይህን ሊያየውና ፕሮግራም ሊሰራበት ይገባል” ብለዋል
➖ ከ25 ጋዜጠኞች የካሜሩን ጉዞ ጋር በተያያዘ የፌዴሬሽኑ ፀሀፊ አቶ ባህሩ ለተጠየቁት ሲመልሱ “ሲሳይ አድርሴ ፕሮሞሽን ስፖንሰር ፈልጎ ሊወስድ ምርጫውን እኛ ልናደርግ ተስማምተን ስራው ተጀምሯል። ነገር ግን ባለቀ ሰአት እንዳልቻለ ነግሮናል የቀረበውን ምክንያት ባናምንበትም አለመሳካቱን አውቀናል በዋናነት ግን ለሚዲያዎቹ ክብር አለን የተባለውን ድርጊት ይፈጽማሉ ብለንም አናምንም” ሲሉ ተናግረዋል።
⚫አሰልጣኝ ውበቱ አባተ በበኩላቸው
➖ “ከኮቪድ መታመስ ጋር ተጨምሮበት በምድብ ጨዋታዎች ላይ እንደነበረው የቡድናችንን የመጨረሻ አቅም አውጥተናል ብለን አናስብም በ2021 የአፍሪካ ዋንጫ ዕቅድ ባናሳካም መልካም ቆይታ ነበረን ብዬ መናገር እችላለሁ በአጠቃላይ ለነበረን ጉዞ ድጋፍ ላደረጉ የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ለሚዲያውና ሌሎች አካላት ምስጋና አቀርባለሁ” ሲሉ ተናግረዋል።
➖ አሰልጣኙ እንዳሉት “ዑጋንዳ የአፍሪካ ዋንጫው ላይ የለችም ነገር ግን ከዩክሬን፣ ኢራቅና ቱርክ ጋር እየተጫወተች ቡድኗን እየገነባች ነው እኛ ግን ራቅ ብለናል..የወዳጅነት ጨዋታ ባለመኖሩ ማግኘት ያለብንን ያህል አልተጠቀምንም በዚህም በቀጣይ እያስተካከልን መሄድ አለብን” ሲሉ ገልፀው
ያለንን ነገር አላስቀጠልንም ማለት ምን ማለት ነው ተብለው ለተጠየቁት በሰጡት ምላሽ
➖ “አለን ያልኩት ቤቴ ኪችን ያለውን ቢሆን ወስጄ አሳይ ነበር ነገር ግን ሜዳ ላይ ነው ያለው ሂድና ጥናት አጥና ብዙ አናሊስቶች ያሉትን ተመልከት መነጽራችንን አውልቀን እውነቱን እንቀበል ኢትዮጵያ ተስፋ የሚያስቆርጥ ነገር የላትም አሁንም የምንፈራው ቡድን የለም ሁሉንም እናከብራለን ፈርተን ግን አንገባም” ሲሉ ተናግረዋል።
➖“ከቫር ጋር ተያይዞ ተጨዋቾቼ ለቫር አዲስ ናቸው ስለማለታቸው የተጠየቁት አሰልጣኝ ውበቱ አባተ
“ልጆችህ ለምን ዝም አሉ ሰውኛ ቅሬታ ለምን አያቀርቡም በማለት አርቢትር በአምላክ ተሰማ ተናግሮኛል ተጨዋቾቼ እያዩ ቅሬታ አለማቅረባቸው ለቫር አዲስ በመሆናቸው አልኩ እንጂ ቫርን እንደምክንያት አላቀረብኩም በዚህ አባባሌ የሚቀልዱ ነበሩ ያው የእውቀት ልዩነት ስለሆነ ብዙም አልተገረምኩም” በማለት አስረድተዋል።
የዝግጅት ቀን ስለማጠሩና ስለ ቀጣይ የአፍሪካ ዋንጫ የመካፈል ዕድላችን የተጠየቁት አሰልጣኝ ውበቱ ሲመልሱ
➖“13 የዝግጅት ቀን ብቻ ልምምድ መስራታችንና ጊዜው ማነሱ ከምድቡ እንዳናልፍ አድርጎናል ብዬ አላምንም ነገር ግን ቀኑ ማጠሩ ተጽዕኖ ነበረው” ሲሉ ተናግረዋል።
አሰልጣኙ ቀጣይ ጊዜን በተመለከተ ሲናገሩ
➖ “በእኔም ይሁን በሌላ አሰልጣኝ በቅርብ ጊዜ ወደ አፍሪካ ዋንጫ እንደምንመለስ ጭላንጭል አይቻለሁ” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
@ ጋዜጠኛ ዮሴፍ ከፈለኝ