ዜናዎች

“ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን መጫወት ትልቅ ክብር እና ኩራት ነው”-ትውልደ ኢትዮጵያዊው ግብ ጠባቂው ዳንኤል ንጉሴ

ትውልደ ኢትዮጵያዊ የ21 ዓመቱ በግብ ጠባቂ ዳንኤል ንጉሴ ትላንት ለኢትዮዽያ ብሔራዊ ቡድን ተሰልፎ ከዕረፍት መልስ በመጫወት የፍፁም ቅጣት ምቱንም መክቷል። ወጣቱ ቁመቱ 1,90 ሜትር ሲሆን ወደፊት ተስፋ ከተጣለባቸው ትውልደ ኢትዮጵያውያን ወጣት ተጨዋቾች አንዱ ነው። በአሁኑ ሰዓት ከኢትዮዽያ ብሔራዊ ቡድን ጋር በአሜሪካ ከሚገኘው ትውልደ ኢትዮጵያዊው ከዳንኤል ንጉሴ ጋር የኢትዮኪክ (ማርታ በላይ) ቆይታ አድርጋለች እንሆ:-
ከግራ ወደቀኝ ( ጋቶች፣ ዳንኤል፣ ዴቪድ በሻህ፣ ማርከስ )
ኢትዮኪክ :-  በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን መካተትና የብሔራዊ ቡድኑን መሊያ ለመጀመሪያ ጊዜ በመልበስህ ምን ተሰማህ?
ዳንኤል:- በጣም ትልቅ ኩራት ነው የተሰማኝ። በቃላት እንኳን ላንቺ ለማስረዳት ያጥረኛል( በፈገግታ) ….ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን መጫወት በጣም ትልቅ ነገር ነው ። ትልቅም ክብር ነውና በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን መሆን ደስ ይላል።
ኢትዮኪክ:- በላውንድ ዩናይትድ ጋር የነበረው። ጨዋታው እንዴት ነበር ? ፍፁም ቅጣት ምትም መልሰካል?
ዳንኤል :- አዎ….ጨዋታው በጣም ደስ ይል ነበረ። ትልቅ አጋጣሚ ነው። ትልቅ ኃላፊነትም ነው ። ከራስ በላይ ብሔራዊ ቡድን መወከል እና ያንን በሚገባ መፈፀም ካዛም ጎን ለጎን ለእኔ ትልቅ ተሞክሮ ነው ያገኘሁት።
ኢትዮኪክ :- እንዲህ ዓይነት አጋጣሚዎች በህይወት ውስጥ ይከሰታል ብለህ አስበህ/ ዓልመህ ታውቃለህ( ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን መመረጡን?
ዳንኤል:- አዎ። በእግር ኳስ ህይወቴ ይሄ አጋጣሚ እንደሚያጋጥመኝ አውቅ ነበረ። ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የመመረጥ ትልቅ ዕልም ነበረኝ እናም ተጀምሯል.. ( በፈገግታ) ።
ኢትዮ ኪክ:- እስቲ ስለ ራስ ትንሽ ንገረኝ ?
ዳንኤል:- የተወለድኩት በኖርዌይ ነው። እናቴ ኢትዮጵያዊ ናት አባቴ ደግሞ ኖሮዌጂያዊ ነው ። ግን አያቶቼ አዲስ አበባ ስላሉ ወደ ስድስት ጊዜ አዲስ አበባ ተመላልሻለሁ። ስለዚህ አዲስ አበባን በመጠኑም ቢሆን አውቃታለሁ። በርግጥ ከተወሰኑ ቃላት ውጪ አማርኛ አልችልም። የምችለው ቃል ሰላም ነህ …እና እንደዚህ ቀላል ነገሮች ነው ( በፈገግታ) ግን አማርኛ ለመማር በጣም እፈልጋለሁ በቅርቡ ተጨማሪ ቃላቶችን አውቃለሁ …(በፈገግታ)።
ኢትዮኪክ: – በብሔራዊ ቡድኑ ውስጥ የአንድ ሳምንት ቆይታህ ጓደኛ አገኘህ?
ዳንኤል :- አዎ….ከዚህ በፊት ማንንም አላውቅም ነበር አሁን ግን ከአብዛኞቹ ጋር የቡድኑ ተጨዋቾን ጋር ተግባብቻለሁ ( በፈገግታ) ….አማርኛ እንዳልኩሽ ባልችልም በእንግሊዝኛ ተግባብተናል ።
ኢትዮኪክ: – በነገራችን ላይ ከዚህ በፊት ግን ስለ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ትሰማ ነበር ወይስ ጨዋታዎች የመከታተል ሁኔታዎች ነበሩህ?
ዳንኤል: – ስለ ብሔራዊ ቡድኑ በፊት በርግጥ በቀጥታ ሳይሆን Highlights. ቪዲዮዎች አይ ነበር። አሁን ያው ቀጥታ እያየሁ። ነው ( በፈገግታ)
ኢትዮኪክ: – የኢትዮጵያ በብሔራዊ ቡድን በFIFA ወርሀዊ ደረጃ በጣም ዝቅተኛ ነው፣ በአፍሪካ ዋንጫና በአለም ዋንጫ ለማለፍ ቡድኑ በጣም ይቸገራል፣ ሌላው ቀርቶ የምስራቅ አፍሪካ ውድድር ለማለፍ ሁሉ ቡድኑ እየተሳነው መጥቷል። አንተ ከምትኖርበት ከአውሮፓ አንፃር ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ለሚመለከታቸው የምትላቸው ነገር ካለ ?
ዳንኤል:- እኔ እንደማስበው ብሔራዊ ቡድኑ ብዙ አቅም ያለው ይመስለኛል። በጣም ትልቅ ብድን ማድረግ ይቻላል። እንደ እኔ ብዬ የምለው ችግሩ ምናልባት መዋቅሩ / Structure/ ፣ አሰራሩ መሠረታዊ እና በጣም ቀላል የሚባለው ነገር ላይ እሱን በሙያተኞች መስራት ይመስለኛል። ሌላው ነገር ችሎታው ሁሉም ነገር ያለ ይመስኛል።
ኢትዮኪክ: – ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ጋር ወደ የፊት ምን ታስባለህ?
ዳንኤል: – እንግዲህ እንደሰማሁት ብሔራዊ ቡድኑ ቀጣይ ጨዋታዎች አሉበት ። ለዛም ጨዋታ እንድሰለፍ ለማድረግ እንደሆነ ነው የተነገረኝ። በርግጥ አላውቅም ግን በቀጣይ የብሔራዊ ቡድኑ ጨዋታዎች ላይ እንደምሰለፍ።
ኢትዮኪክ: – አሁን ላይ ስለምትጫወትበት የኖርዌው ክለብ እና በክለቡ ውስጥ በቋሚ አሰላለፍ ያለህ ያንተ ቦታህ ?
ዳንኤል :- የምጫወት ለሁለተኛ ዲቪዚዮን ክለብ ነው። የክለቡ ስም ( Bærum SK ) ይባላል። እኔ ደግሞ ከቋሚ 11 ተሰላፊዎች አንዱ ነኝ።
ኢትዮኪክ: – ለኖርዌይ ብሔራዊ የመመረጥ ዕድል አግኝተህ ታውቃለህ?
ዳንኤል :- አዎ። ለዋናው ብሄራዊ ቡድኑ ማለቴ ለኖርዌ ከ16 ዓመት በታች ዕድሜ ላይ ተጠርቼ ነበር ። ማለት ለዋናውን ሆኖ ግን ከዋናው ቀጥሎ በተጠባባቂነት የሚጠሩ ተጨዋቾች አሉ በዛ ውስጥ ተካትቼ ነበር። በተጨማሪም ከ18 ዓመት በታች በትክክል ከተመረጡት ውስጥ ተጠርቼ ነበር አጋጣሚ በጉዳት መጫወት ሳልችል ቀርቻለሁ።
ኢትዮኪክ :- አሁን ላይ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጠርተሃል በቀጣይ ለኖርዌ ብሔራዊ ቡድን የመጠራት ዕድሉን ብታገኝ የትኛውን ትመርጣለህ?
ዳንኤል :- …. አሁን ያለሁት አዚህ ነው ስለዚህ እዚሁ የሚቀረው …ምን ይመስልሻል ….በፈገግታ አዎ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን እመርጠለሁ….
ኢትዮኪክ: – ከእግርኳስ ጎን ለጎን ዳንኤል ትምህርትስ ይማራል ?
ዳንኤል: – በ IT ( Information Technology ) ዲግሪዬን ለማግኘት በትርፍ ጊዜዬ እማራለሁ ። ሦስት ዓመት ተምሪያለለሁ ሁለት ዓመት ይቀረኛል ።
ኢትዮኪክ: – ዳንኤል ስለነበረን ቆይታ አመሠግናለሁ
ዳንኤል: – እኔም አንችን ማርታ አመሰግናለሁ ።

One thought on ““ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን መጫወት ትልቅ ክብር እና ኩራት ነው”-ትውልደ ኢትዮጵያዊው ግብ ጠባቂው ዳንኤል ንጉሴ

Comments are closed.