ቤትኪንግ ፕሪሜር ሊግ ዜናዎች

“ለሀዲያ ደጋፊዎች ትልቅ ክብር አለኝ ፣ለደጋፊዎች ፣ለአሰልጣኞች እና ለተጨዋቾቹ ከልቤ ይቅርታ እጠይቃለሁ ዳንሱ ለ(ጆን) መታሰቢያነት ነበር ” ኤፍሬም አሻሞ

በ22ኛ ሳምንት የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ ሀዋሳ ከነማ ተጋጣሚውን ሀዲያ ሆሳዕናንን ሶስት ለባዶ በማሸነፉ ይታወሳል። በወቅቱ በጨዋታው ላይ የሐዋሳዎቹ ኤፍሬም አሻሞ ጎሉን አስቆጥሮ ደስታውን የገለፀበት መንገድ የሀዲያ ሆሳዕና ደጋፊዎችን አስቆጥቷል።እንደሚታወቀው ኤፍሬም አሻሞ ቀደም ባሉት ጊዜያት ጎሎችን ከመረብ ሲያስቆጥር በሚያሳየው የደስታ አገላለፁ ይታወቃል። ይህም ከታላቅ ወንድሙ የወረሰው ሲሆን
የቀድሞው የሀዋሳ ከነማ ተጫዋች የሆነበረው ጌታሁን አሻሞ (ጠገራ) የኤፍሬም አሻሞ እና የብርሃኑ አሻሞ ታላቅ ወንድም ነው። የአሻሞ ልጆች ከታላቅ ወንድማቸው የኳስን ጥበብ ብቻ ሳይሆን በሜዳ ላይ ጎል ካስቆጠሩ በኃላ በሚያሳዩት ለየት ባለ የደስታ አገላለፅንም ይታወቃሉ።
 ከቀናት በፊት ሐዋሳ ከተማ ከሀዲያ ሆሳዕና ባደረጉት ጨዋታ  ኤፍሬም አሻሞ ባስቆጠረው ጎል ከሶስት ዓመት በፊት የሞተውን -ጆንን ለማስታወስ ያሳየው የደስታ አገላለፅ ሀዲያዎችን አሰከፍትዋል።  ኤፍሬም አሻሞ ከኢትዮኪክ ጋር ባደረገው ቆይታ ለሀዲያ ሆሳዕና ክለብ ተጨዋቾች ፣ አሰልጣኞች እና የክለቡ ደጋፊዎችን በይፋ ይቅርታ ጠይቀዋል።ከኤፍሬም አሻሞ ጋር በዚህ ጉዳይ ዙሪያ ያደረግነውን ልዪ ቆይታ እንሆ :-
ኢትዮኪክ -:- በዳንስ (ደሰታ) አገላለፅህ ዙሪያ ብዙዎች አዝነዋል ኤፍሬም በዚህ ላይ ምን ሃሳብ አለው ?
ኤፍሬም :- የደስታ አገላለፄን ምናልባትም በተቃራኒው መንገድ ያዮት ደጋፊዎችና ያዘኑም እንዳሉ ተረድቻለሁ። በዚህ መልኩ ደስታዬን ስገልፅ የመጀመሪያ አይደለም። ከዚህ በፊትም ደደቢት ሆኜ በተመሳሳይ መልኩ ይህንኑ አድርጊያለሁ። በወቅቱ ያን ሳደርግ ማንም በተለየ መልኩ አልወሰደውም። አሁን ላይ በዚህ መልኩ መተርጎሙ አስደንግጦኛል። እኔ ከሀዲያ ሆሳዕና አሰልጣኝ እና ቡድኑ ጋር ምንም ሊያገናኝ የሚችል ነገር የለውም።
ኢትዮኪክ – ስለ ዳንሱ የተለየ ትርጓሜ ንገረኝ ?
ኤፍሬም :- ከሀዲያ ጋር በነበረን ጨዋታ ጎል አስቆጥሬ የደነስኩት ዳንስ የምወደውን ውሻ ለማስታወስ ነበር ። የምወደው ውሻዬ -ጆን ከሞተ ከሶስት ዓመት በፊት ሲሆን እኛ ሀገር የውሻ ህክምና ብዙም ስላሌለ በመረዝ ምናምን ነው ውሻዬን የገደሉት። በእርግጥ እኛ ሀገር ለውሻ የሚሰጠው ክብር ምንም አይደለም። ውሻ በብዙ መልኩ ታማኝ እና የሰውን ህይወት ሲያተርፍ ፣ብዙ ነገሮች ሲያደርግ በጥሩ ታማኝ ጓደኛነትም  ይታወቃል ። የእኔም ውሻ ጆን ይባላል። እናም የምወደውን ውሻዬ (ጆን )ከሞተ በኋላ በየዓመቱ ትዝ ስለሚለኝ ፣ ጎል ሳገባ ለእሱ መታሰቢያ እንዲሆን ነው ዳንሱ እንጂ ሌላ ምንም ትርጉም የለውም።
ኢትዮኪክ :- የደነስከው ዳንስ የሃዲያ ሆሳዕና ክለብ ክብር ለመንካት ነው ስለሚባለውስ ኤፍሬም በዚህ ላይ ምን ሃሳብ አለው ?
ኤፍሬም :- ኸረ በጭራሽ ! ሲጀምር እኔ እራሴ ቤተሰቦቼ ሀዲያ ናቸው ፣ የዘር አረጌ ሀዲያ ነው። በርግጥ ተወልጄ ያደኩት ሀዋሳ ቢሆንም አባቴ ሀዲያ ነው ። ለሀዲያ ህዝብና ለክለቡ እጅግ ሲበዛ ትልቅ ክብር አለኝ። ስለዚህ ከክለቡ ጋር ምንም የሚያገኘው ነገር እንደሌለ ደጋግሜ ለመናገር እፈልጋለሁ። ከአሰልጣኙ ወይም ከቡድኑ ጋር ምንም የሚያገናኝ ነገር የለም። በየዓመቱ ጎል ሳስቆጥር ቀን አለው ፤ በአጭሩ የሞተውን ውሻዬን ለማስታወስ ብዬ ነው እንጂ ፡ የሀዲያ ሆሳዕና ደጋፊዎችንና ተጨዋቾችን ለማንቋሸሽ አስቤ እንዳልሆነ እንዲረዱልኝ እጠይቃለሁ።በአንዳንድ ሰዎች ከተጋጣሚ ቡድን ጋር ለማጋጨት የሚደረጉት ጥረቶችን አይቼ እጅግ ከልቤ አዝኛለው። ለሀዲያ ቡድን ተጫዋች እንዲሁም ደጋፊዎች ትልቅ ክብር አለኝ።
ኢትዮኪክ -:ምናልባት ክለቡ በወቅቱ በጎዶሎ ተጨዋቾች እና ችግር ላይ ከመሆኑ አንፃር ዳንሱ ተገቢ ነበር ?
ኤፍሬም -;- ለክለቡም ለአሰልጣኝቹ እና ለተጨዋቾቹም ከፍተኛ ክብር አለኝ ።በእንደዚህ አይነት ወቅት እንደዚህ ዓይነት ስሜት ውስጥ ሆነው ይህን በማድረጌ ስህተት ነው ። ይሄ ነገር መግነኑ ትንሽ እነሱን ያስቆጣ ስለሆነ ለዚህ ደግሞ  ለክለቡም ፣ ለአሰልጣኝቹ እና ለተጨዋቾቹም ከልቤ ይቅርታ እጠይቃለሁ። ግን በወቅቱ ያ ነገር ውሻዬን (ጆን) መታሰቢያነት ስለመጣለኝ ለማድረግ በሚል ብቻ መሆኑን እንዲረዱልኝ እጠይቃለሁ።
ኢትዮኪክ -: ስለዚህ ኤፍሬም ለሀዲያ ሆሳዕና በአጠቃላይ ይቅርታ ይጠይቃል ?
ኤፍሬም -: አዎ ! እኔ የምወደውን ውሻዬ- ጆንን ለማስታወስ ስለፈለኩ እንጂ ሌላ ነገር አልነበረም። ቢሆንም ደጋፊው እና ክለቡን ይቅርታ እጠይቃለሁ። እኔ በመደነስ እና ሌላ ነገሮች በማድረግ እንደምታውቅ የኢትዮጵያ የስፓርት አፍቃሪ ያውቃል። ደጋፊዎች በሌላ እንዳይወስዱብኝ በድጋሚ ይቅርታ እጠይቃለሁ።

One thought on ““ለሀዲያ ደጋፊዎች ትልቅ ክብር አለኝ ፣ለደጋፊዎች ፣ለአሰልጣኞች እና ለተጨዋቾቹ ከልቤ ይቅርታ እጠይቃለሁ ዳንሱ ለ(ጆን) መታሰቢያነት ነበር ” ኤፍሬም አሻሞ

Comments are closed.